Wednesday, August 23, 2017

መታወቅ ወይስ ማወቅ?

. . . . . . . . በዚያ ጊዜ፣ ‘ከቶ አላወቅኋችሁም፤ እናንት ክፉዎች፤ ከእኔ ራቁ’ ብዬ በግልጽ እነግራቸዋለሁ። ማቴዎስ 7: 23
በመጀመሪያ የዚህ ጽሑፍ ዓላማ ማንንም ቡድን ወይም ግለሰብ ለመንቀፍ ወይም የማንም ትምህርት ላይ ጣት ለመቀሰር እንዳልሆነ ለአንባቢዎቼ ለማስገንዘብ እፈልጋለሁ። የዚህ ጽሑፍ ዋና ዓላማ ያለንበት ዘመን የመጨረሻው ዘመን መሆኑን ግነዛቤ ውስጥ በማስገባት ቀለል ባለ ገለጻ የራሴን እይታ ለማስተላለፍና ሌሎችንም ለማነጽ ነው።

“አላወቅኋችሁም” የምትለውን ቃል በጣም የምፈራት ይህን ቃል ሳነብ ነው። ምክንያቱም አውቀዋለሁ የምንለው ሁሉ እኛን ላያውቅን እንደሚችል እንዳስበው ስላምታስገድደኝ ነው። ለምሳሌ ብዙ ታዋቂ ሰዎችን ብዙ ጊዜ በተለያየ መገናኛ ብዙሃን ስለምናያቸው ወይም ስለነሱ ማንበብ ስለቻልን የምናውቃቸው ያህል ይሰማናል። በእርግጥ ይህ አይነት ዕውቀት ራሱን የቻለ ደረጃ ያለው ዕውቀት ነው። ከዚህ አልፈን ዕውቀትን መተንተን የዚህ ጽሁፍ ዓላማ ስላልሆነ በዚሁ እንለፈው። ከዛም አልፈን በደንብ ቀረብ ብለን የምናውቃውቸው ሰዎች ይኖራሉ፣ ምን እንደሚወዱ ምን እንደሚጠሉና ከዛም ዘልቀን የግል ጉዳያቸውንም ሳይቀር ጠንቅቀን የምናውቅላቸው ሰዎች እኛን ያውቁናል ብለን በልበ ሙሉነት የምንናገርላቸው ሰዎች ይኖሩ ይሆናል።

አንድን ሰው ያወቅነው ስለመሰለን ወይም በደንብም ስላወቅነው በእርግጠኝነት ያ ሰው እኛን ያውቀናል ማለት አይቻልም። ጉዱ የሚታየው ስለማውቃቸው ያውቁናል ብለን ያሰብናቸው ሰዎች ስለኛ ሲጠየቁ ስለኛ ጠንቅቀው አውቀው መመለስ መቻላቸውን ስናረጋግጥ ብቻ ነው። ባጭሩ ያወቅነው የመሰለንን ነገር ሁሉ አውቀነዋል ማለት እንደማይቻል ሁሉ ፤ ያወቅነው ሁሉ አያውቀነም። ለዚህም ነው፣ “አላወቅኋችሁም” የምትለውን ቃል በጣም የምፈራት ይህን ቃል ሳነብ ነው ያልኩት።

በማቴዎስ 7 እና 25 ላይ የምናነበው የመጨረሻ ፍርድ በሚሆንበት ጊዜ የሚከሰተውን ሁኔታ ነው። በዚያም “አላወቅኋችሁም” የሚባሉት ሰዎች ”ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ“ ብለው የሚጠሩቱ፣ አጠራራቸውም የሚመስለው “እንዴ እኛኮ እናውቅሃለን ከማወቅም አልፈን እኮ በስምህ ብዙ ሰርተናል፣ ስላንተ እኮ ብዙ አውርተናል” የሚል ነው። ምስክሮች ኧረ አሉን የሚሉም ይመስላሉ። በተቃራኒው ደግሞ “አውቄያችኋለው” የተባሉቱ “እንዲህ አርገን ነበር እኮ፣ እንዲህ ብለን ነበር እኮ” እያሉ ሲደክሙ አይሰሙም። ኧረ ማድረጋችንንም አናስታውስም ነው የሚሉት።

በዘመናችንም ይህ ታሪክ እየተሰራ ያለ ይመስላል። በተለይም የኢንፎርሜሽን ዘመን ከመሆኑ የተነሳ እንዲሁም የማህበራዊ መገናኛዎች መፈጠርና በቀላሉ ለብዙሃኑ በአንድ መድረክ ብቻ መደረስ የሚቻልበት ዘመን ላይ ስለደረስን እዩኝ እዩኝ ማለት የጊዜያችን ትልቁ ፈተና ነው። በአሁኑ ዘመን እራሳችንን በራሳችን ቀድተን የምንኖርበትን ቤት ይሁን፣ የለበስነውን ልብስ ወይ የምንነዳውን መኪና ይሁን ወይ ቁመናችንን ለማሳየት ግልጽ ባልሆነ መልኩ እዚህ ግቡ የማይናሉ ዓላማቸው ምን እንደሆነ የማይታወቁ መልዕክቶችን ማስተላለፍ የጊዜው ብሂል ከሆነ ቆይቷል። ከዛም አልፎ የቴሌቪዥን አገልግሎት ከሌላችሁ ወንጌል መስበክ አይቻልም የተባለ እስኪመስል ድረስ  ብሎ መናገር የማይከብድበት ጊዜ ሆኗል። ኧረ ይሄ ነገር ልክ አይደለም ብሎ ሃሳብ መሰንዘር ጊዜው እንዳለፈበት ሰው አስቆጠሮ “እንዴ ወጣት አይደለህ፣ እንዴ አራዳ መስለኽኝ፣ ውይ የክፍለ ሃገር ልጅ ነህ እንዴ” የሚያስብልበት ደረጃ ደርሰናል።

እነዚህ “አላወቅኋችሁም” የተባሉ ሰዎች በእርግጠ ስለ ክርስቶስ ብዙ የሚያወሩ፣ ከዛም አልፈው ተዓምራትና ድንቅ የሚፈጽሙ ኧረ እንዳውም በስሙ ሁሉ አጋንንት የሚያስወጡ ናቸው። ታዲያ እንዲህ ማለትህ በዚህ ዘመን የምናያቸው ይህን አይነት ነገር የሚያደጉ ሰዎች “አላወቅኋችሁም” ይባላሉ ልትለን ነው ብላችሁ መጠየቃችሁ ደግ ነው። እንግዲህ ከጠየቃችሁ መልስ ብዬ የምሰጣችሁ የሚከተለውን ይሆናል።

በክርስቶስ ዘንድ የሚታወቁትንና የማይታወቁትን ለመለየት መልሱን የምናገኘው በዛው በማቴዎስ 7 እና 25 ላይ ነው።
በማቴዎስ 7 15 — 18 “በውስጣቸው ነጣቂ ተኵላዎች ሆነው ሳሉ የበግ ለምድ ለብሰው መካከላችሁ በመግባት ከሚያሸምቁ ሐሰተኛ ነቢያት ተጠንቀቁ። ከፍሬያቸው ታውቋቸዋላችሁ፤ ከእሾህ ቍጥቋጦ ወይን፣ ከኵርንችትስ በለስ ይለቀማልን? እንዲሁም ጥሩ ዛፍ ሁሉ ጥሩ ፍሬ፣ መጥፎ ዛፍ ግን መጥፎ ፍሬ ያፈራል። ጥሩ ዛፍ መጥፎ ፍሬ፣ መጥፎም ዛፍ ጥሩ ፍሬ ማፍራት አይችልም። 

ከፍሬያቸው ታውቋቸዋላችሁ ሲለን ስለ ክርስቶስ ብዙ የሚያወሩ፣ ከዛም አልፈው ተዓምራትና ድንቅ የሚፈጽሙ እና በስሙ አጋንንት የሚያስወጡ ሁሉ በደፈናው “አላወቅኋችሁም” ይባላሉ ብዬ አላምንም። ነገር ግን እንዲህ ማድረግ በራሱ ብቻ ፍሬ እንዳልሆነ ያሳየናል እንጂ። ፍሬ ለማየት ጊዜ ወስዶ መከታተል ይጠይቃል።

ለኔ “አላወቅኋችሁም” ይባላሉ ብዬ የማምነው፥
1 ከክርስቶስ ወንጌል ይልቅ የሰውን ፍልስፍና ወይም መጽሓፍ አንብበው እኔን የገባኝ ካልገባችሁ የሚሉ ወንጌል ሳይሆን ግን የሚመስል ፍልስፍና ይዘው ሌላው ካልገባው ብለው በየሰፈሩና በየአገሩ እየዞሩ ወንጌልን የሚሸቅጡ፤
2 ከክርስቶስ ስም ይልቅ ለራሳቸው ስምና ማዕረግ ብዙ የሚተጉ፣ ምስላቸውን በየቦታው በመለጠፍ ለመታየት የቋመጡ እና የነሱ አስተምህሮ ብቻ እንዲሰማ የሚሯሯጡ፤
3 በትምህርታቸው ላይ ጥያቄ ያነሳን በፍጥነት የሆነ ጎራ ጋ ወስደው የሚፈርጁ፣ ከቻሉም እኔን ከተቃወምክ ትሞታለህ ወይ እግዚአብሄር ይቀጣሃል ከማለት የማይቆጠቡ ደፋሮች፤
4 ነገራቸው ሁሉ ከገንዘብ ጋር የተቆራኘ፣ ብልጣልጥ በሆነ አቀራረብ በትምህርታቸው የሰውን ስሜት አስደስተው ከቻሉ ከየቤተክርስቲያኑ ሰዎች አፈናቅለው የራሳቸውን ቤተክርስቲያን ለመትከል ወደኋላ የማይሉ፣ ካልቻሉ አይን ባወጣ መልኩ ገንዘብ ጠይቀው ሰብስበው የሚሄዱ፤
5 ከእውነተኛው የእግዚአብሄር ቃል ይልቅ ለሰዎች የሚመች ስኬት የማግኛ፣ ከድህነት ማምለጫ፣ ከበሽታ መዳኛ እና የመሳሰሉ ምድር ተኮር ጉዳዮች ላይ በሰፊው ጊዜ የሚያጠፉ፤ ከወንጌል ይልቅ ስሜት አነቃቂ የሆኑ አስተምህዎች ላይ ያተኮሩ motivational speaking)
6 ፍሬ ብለው የሚያሳዩት ምን ያህል ገንዘብ እንዳላቸው፣ ምን ያህል አባል እንደመዘገቡ፣ ምን ያህል በዓለም ላይ ዝናን እንዳገኙ ሲሆን፣ በኛ ትምህርት ወይ ተዓምራት ጌታን የተቀበሉ እያሉ ባልለፉበት ነገር የሚመጻደቁና የቁጥር ስሌት ማሳየት የሚወዱ……. “ያልደከማችሁበትን እንድታጭዱ ላክኋችሁ፤ አድካሚውን ሥራ ሌሎች ሠሩ፤ እናንተም የድካማቸውን ፍሬ ሰበሰባችሁ።” ዮሓንስ 438
7 ያለምንም ማስረጃ በድፍረት እግዚአብሄር እንዲህ ብሎኛል የሚሉና፣ መረጃና መሰረት የሌለው ወሬ በድፍረት የሚያወሩ፤
8 ለሚያምነውም ለማያምነውም ተዓምራት ማድረግና ትንቢት መናገር የሚያዘወትሩና፣ መጽሓፍ ቅዱስን ለራሳቸው የውሸት ትምህርት እንደ ደጋፊ የሚወስዱ እንጂ ላነበቡት መጽሓፍም ይሁን ለተገረሙበት ፍልስፍና መጽሓፍ ቅዱስን እንደ መመረመርያ የማይጠቀሙ።

በተቃራኒው “ኑ እናንተ የአባቴ ብሩካን“ የተባሉት፥
1 ለማዕረጋቸው የማይጨነቁ፣ ከራሳቸው ስም ይልቅ ለክርስቶስ ስም የሚሞቱ፣ ልታይ ልታይ የማይሉ፣
2 ሰው የማያውቃቸው ብቻ ሳይሆኑ የሚያደርጉትን ነገር እንኳን የተለየ እንዳልሆነ የሚሰማቸው፣
3 ብልጣልጥነት የማይገባቸው፣ ነገራቸው ሁሉ ከገንዘብ ጋር ያልተቆራኘ፣ ሃብታም የመሆን ከባድ ምኞት የሌላቸው፣
4 ተዓምራትና ድንቅን በየቦታው እየዞሩ የማይከተሉ፣ ምድር ጊዜያዊ መኖርያቸው መሆኑን ስለተረዱ የዚህ ዓለም ጥቅማ ጥቅም የማያታልላቸው፣
5 የክርስቶስ አምባሣደር እንደሆኑ ስለገባቸው እራሳቸውን ከማንም ቡድን ይሁን ተቋም ጋ የማያቆራኙ፣
6 እንደ ክርስቶስ መኖር የህይወታቸው ዘይቤ ስለሆነ ለሚያደርጉት ነገር ማስረጃ እንኳን የማይሰበስቡ፣ ቁጥር እያሰሉ በኔ አገልግሎት ይህን ያህል ሰው እንዲህ ሆነ የማይሉ ‘ጌታ ሆይ፤ ተርበህ አይተን መቼ አበላንህ? ወይም ተጠምተህ አይተን መቼ አጠጣንህ? እንግዳ ሆነህ አይተን መቼ ተቀበልንህ? ወይስ ታርዘህ አይተን መቼ አለበስንህ? እንዲሁም ታመህ ወይም ታስረህ አይተን መቼ ጠየቅንህ?’ በማቴዎስ 25 37᎐39 ብለው የጠየቁ።


ከዚህም በላይ ለሁለቱም ጎራ ዝረዝር ማውጣት ይቻላል። ዋናው ጥያቄ ግን እኔስ የት እሆን ያለሁት ብሎ መጥየቅ ነው። እግዚአብሔር ባስቅመጠን ቦታ ላይ ሆነን የእነ እከሌ መታወቅ አስደምሞን እኔም ካልታወኩ ብለን ከተቀመጥንበት ቦታ ተነስተን እንደ ዝንጉዎቹ ልጃገረዶች ዘየት ልንገዛ ስንሄድ በድንገት ሙሽራው መጥቶ ከሰርጉ እንዳንቀር እግዚአብሔር ይርዳን።  

Thursday, August 17, 2017

በእርግጥ መጽሐፉ ምን ይላል?

ለዚህ ጽሑፍ ምክንያት የሆነኝን ጉዳይ አንስቼ ልጀምር። በቅርቡ ከአንድ የቅርብ ወዳጄ ጋር ሆነን ስለ ብልጽግና ወንጌል እንዲሁም አሁን በኢትዮጵያ ውስጥ ስለተስፋፋው ”የነብያት“ እንቅስቃሴ አንስተን ስንጫወት የሊሊ መዝሙር እንደ አንድ ጥሩ መልስ መቅረቡ ስላስገረመኝ እስኪ ምንአልባት ይህ ጉዳይ ለብዙዎች የመነጋገርያ ጉዳይ ስለሆነ በሰፊው ልምጣበት ብዬ ይህን ጽሁፈ ጫር ጫር እንዳደርግ ምክንያት ሆነኝ።

ከአንኳሩ ጉዳይ ልጀምርና ፤ የትኛውንም የክርስትና አስተምህሮ መመዘን ያለብን በምንድን ነው የሚለውን ጥያቄ በአጭሩና በማያሻማ መልኩ ስንመልሰው በመጽሓፍ ቅዱስ ብለን ነው። ለዚህም ነው ወንድሜ በመዝሙር መልስ ለመስጠት ሲታገል ሳየው ያሳዘነኝ። መጽሓፉ በእርግጥ ምን ይላል አትታመሙም፣ አትደኽዪም፣ ችግር ወይም መከራ አያገኛችሁም፣ አተጎሳቆሉም፣ አትሞቱም ይላል ሃብት በምድር አከማቹ፣ ጤነኞች ካልሆናችሁ ስለመዳናችሁ ተጠራጠሩ፣ ችግር ወይም መከራ ከመጣባችሁ የኔ ደቀ መዛሙርት ላለመሆናችሁ ምልክት ይሁን፣ ደግሞም የምን መጎሳቆል እንደዛማ ከሆናችሁ የኔ አይደላችሁም ይላል

በእርግጥ መጽሓፉ ምን ይላል እኔ ክርስቶስን እንደምመስል እናንትም እኔን ምሰሉ ሲል ጳውሎስ ፤ ክርስቶስ በእርግጥ በምድር ሳለ በምድራዊ ቁሳቁስ ልቡ ተይዞ በዘመኑ አንደኛ የተባለ መኖርያ ቤት ውስጥ ይኖር ነበር፣ ሲጓጓዝም ምርጥ ምርጥ ጀልባዎች ላይ ይሳፈር ነበር እንዳውም አብዛኛዎቹ ጀልባዎች የግሎቹ ነበሩ፣ ደቀ መዛሙርቱም ዋናው ስራቸው የእርሱ ክቡር ዘበኛ መሆን ነበር፣ ከህዝብ በተሰበሰበ ገንዘብ የተሰራ በጊዜው አለ የተባለ መድረክ ላይ ነበር ትምህርት የሚያስተምረው ማለቱ ይሆን

በእርግጥ መጽሓፉ ምን ይላል ኧረ እንዳውም እኔ ስሄድ በእኔ ስም ህዝብ ሰብስባችሁ ሰዎችን ሰብስባችሁ ደስ ደስ የሚሉ ቃላቶች የሞሉባቸውን ትምህርቶች እያስተማራችሁ፣ አጋንንት በስሜ እያስወጣችሁ፣ ሰዉን ስጋዊ ፈውስ ብቻ እየፈወሳችሁ፣ ከቻላችሁ በዶላር ካልቻላችሁም ደግሞ በብር ገንዘብ እየሰበሰባችሁ ጠብቁኝ፣ ስመጣ ሂሳብ አወራርዳለሁ ይላልበእርግጥ መጽሓፉ ይህን ይላል
በእርግጥ መጽሓፉ ምን ይላልከእናንተ ላነሰው ለዛ ወንደማችሁ ወይም እህታችሁ ካልቻላችሁ በፌስ ቡክ ከቻላችሁ በራሳችሁ ቴሌቪዥን ምን ያህል ከሌላው የተሻለ ዕውቀትና የኑሮ ደረጃ እንዳላችሁ ጉራችሁን እየዘራችሁ ጠብቁኝ እንጂ የምን የተራበ ማብላት፣ የተጠማ ማጠጣት፣ የታረዘ ማልበስ ነው ለዛውም ማንም ሳያያችሁ፣ ሳይጨበጨብላችሁ ይል ይሆን  

በእርግጥ መጽሓፉ ምን ይላልእንኳን ካላችሁ ላይ ልትሰጡ ቀርቶ ከቻላችሁ በተዓምር ብር አባዝታችሁ ካልሆነም በእኔ ስም ተከልላችሁ ምንም የማያውቁትን የዋሆች አሳምናችሁ በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ በምድር አከማችታችሁ የሚያማምሩ ልብሶችንና  መኪናዎችን በየቀኑ እያቀያየራችሁ በሃብት ሰክራችሁ ስስትን ጠግባችሁ እኔን ከማያውቁኝና ከፈሪሳውያን በልጣችሁ ካልጠበቃችሁኝማ እኔም በተራዬ አላውቃችሁም እላችኋለሁ ይል ይሆን  

በእርግጥ መጽሓፉ ምን ይላልእስቲ እኔ ከምነግራችሁ እራሱ መጽሓፉን ምን እንደሚል አብረን አናነበውም።
ዮሐንስ 16: 33 “በእኔ ሰላም እንዲኖራችሁ፣ ይህን ነግሬአችኋለሁ። በዓለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ፤ ነገር ግን አይዞአችሁ፤ እኔ ዓለምን አሸንፌዋለሁ።
ማቴዎስ 10: 38-39 መስቀሉን ተሸክሞ የማይከተለኝ የእኔ ሊሆን አይገባውም። ሕይወቱን ሊያድን የሚፈልግ ያጠፋታል፤ ሕይወቱን ስለ እኔ አሳልፎ የሚሰጥ ግን ያገኛታል።
ሮሜ 8: 35 ከክርስቶስ ፍቅር የሚለየን ማን ነው? ችግር ነው ወይስ ሥቃይ፣ ወይስ ስደት፣ ወይስ ረሀብ፣ ወይስ ዕራቍትነት፣ ወይስ አደጋ ወይስ ሰይፍ?
1 ጴጥሮስ 4: 1 እንግዲህ ክርስቶስ በሥጋው መከራን ስለ ተቀበለ እናንተም በዚሁ ዐላማ ታጥቃችሁ ተነሡ፤ ምክንያቱም በሥጋው መከራን የሚቀበል ሰው ኀጢአትን ትቶአል።
1 ጴጥሮስ 3 : 13,14 መልካም ነገር ለማድረግ ብትቀኑ የሚጐዳችሁ ማን ነው? ነገር ግን ስለ ጽድቅ እንኳ መከራ ቢደርስባችሁ ብፁዓን ናችሁ፤ “ዛቻቸውን አትፍሩ፤ አትታወኩም።” 
ገላትያ 6: 2-3አንዱ የሌላውን ከባድ ሸክም ይሸከም፤ በዚህም ሁኔታ የክርስቶስን ሕግ ትፈጽማላችሁ። አንድ ሰው ምንም ሳይሆን ትልቅ የሆነ ቢመስለው ራሱን ያታልላል። 
ፊልጵስዩስ 1: 29-30 በክርስቶስ እንድታምኑ ብቻ ሳይሆን ስለ እርሱ መከራ እንድትቀበሉም ይህ ጸጋ ተሰጥቶአችኋልና፤ ቀድሞ እንዳያችሁት አሁንም በእኔ እንዳለ በምትሰሙት በዚያው ዐይነት ተጋድሎ እናንተም እያለፋችሁ ነውና።
1 ጴጥሮስ 2: 21የተጠራችሁትም ለዚሁ ነው፤ ምክንያቱም ክርስቶስ ስለ እናንተ መከራን የተቀበለው የእርሱን ፈለግ እንድትከተሉ ምሳሌን ሊተውላችሁ ነው።
ሮሜ8: 18የአሁኑ ዘመን ሥቃያችን ወደ ፊት ሊገለጥ ካለው ለእኛ ከተጠበቀልን ክብር ጋር ሲነጻጸር ምንም እንዳይደለ እቈጥራለሁ።
ማቴዎስ 7: 21 - 23 “በሰማይ ያለውን ያባቴን ፈቃድ ሳይፈጽም ‘ጌታ ሆይ፤ ጌታ ሆይ፤’ የሚለኝ ሁሉ ወደ መንግሥተ ሰማይ አይገባም። በዚያ ቀን ብዙዎች፣ ‘ጌታ ሆይ፤ ጌታ ሆይ፤ በስምህ ትንቢት አልተናገርንምን? በስምህ አጋንንት አላወጣንምን? በስምህስ ብዙ ታምራት አላደረግንምን?’ ይሉኛል። በዚያ ጊዜ፣ ‘ከቶ አላወቅኋችሁም፤ እናንት ክፉዎች፤ ከእኔ ራቁ’ ብዬ በግልጽ እነግራቸዋለሁ።

በመጨረሻብ ማቴዎስ 25 ላይ ከቁጥር 23 ጀምሮ እስከ 46 ያለውን እራሳችሁ እንድታነቡ እየጋበዝኩ፡ እንደ ማጠቃለያ በዘመናችን ለተከሰቱት አዲስ ለሚመስሉ ነገር ግን ከነጳውሎስ ዘመን ጀምሮ ለነበሩ እንግዳ መሰል አስተምህሮዎች እጃችንን ከመስጠታችን በፊት በእርግጥ መጽሓፉ ምን ይላል ብለን መጠየቅ እንጂ እነ እከሌ እኮ እንዲህ ብለው ዘምረዋል እንዲህ ብለው አስተምረዋል በማለት ለጆሮዋችን በሚመች መልኩ የመጣውን ትምህርት ይሁን ትንቢት አስተናጋጆች እንዳንሆን እንጠንቀቅ። ይልቁን የዘመኑ ትምህርትና ትንቢት ምነው የተራራውን ስብከት የሚሰብክ እና የሚተነብይ ያልሆነው ምነው ዝቅ በሉ፣ ታገሱ፣ በጽድቅ ኑሩ፣ ያላችሁን ስጡ፣ የተገፉትን ፈልጉ፣ልታይ ልታይ ከማለት ተቆጠቡ የሚል ትምህርት እና ትንቢት የሞኝነት ያህል የተቆጠረው እንዳያሰናክሏችሁ ከዚህ ዓለም ተግዳሮቶች ተጠበቁ ሳይሆን በዓለም እንደ ድል አድራጊነት የሚያስቆጥሩት ቁሳቁስ እና ገንዘብ ታገኛላችሁ ይሆንላችኋል ይሳኩላችኋል ላይ ብቻ ተነጠለጠሉ ይህን መጠየቅ በዘማናዊ ክርስትና ለተጠመቁት እንደ ሞኝነት ነውም አይደል


በእርግጥ መጽሓፉ ምን ይላልአትታመሙም፣ አትደኽዪም፣ ችግር ወይም መከራ አያገኛችሁም፣ አተጎሳቆሉም፣ አትሞቱም ይላል ሃብት በምድር አከማቹ፣ ጤነኞች ካልሆናችሁ ስለመዳናችሁ ተጠራጠሩ፣ ችግር ወይም መከራ ከመጣባችሁ የኔ ደቀ መዛሙርት ላለመሆናችሁ ምልክት ይሁን፣ ደግሞም የምን መጎሳቆል እንደዛማ ከሆናችሁ የኔ አይደላችሁም ይላል

እንደዛማ ከሆነ ብልጽግና ወንጌልን ብልጥ - ግና ብለን ብንጠራው ይሻል ይሆን