Friday, October 9, 2020

ጥብብ ……………. ለምን?

 1 ቆሮንቶስ 1፡18 — 31 

18 የመስቀሉ ቃል ለሚጠፉት ሞኝነት፥ ለእኛ ለምንድን ግን የእግዚአብሔር ኃይል ነውና።
19 የጥበበኞችን ጥበብ አጠፋለሁ የአስተዋዮችንም ማስተዋል እጥላለሁ ተብሎ ተጽፎአልና።
20 ጥበበኛ የት አለ? ጻፊስ የት አለ? የዚች ዓለም መርማሪስ የት አለ? እግዚአብሔር የዚችን ዓለም ጥበብ ሞኝነት እንዲሆን አላደረገምን?
21 በእግዚአብሔር ጥበብ ምክንያት ዓለም እግዚአብሔርን በጥበብዋ ስላላወቀች፥ በስብከት ሞኝነት የሚያምኑትን ሊያድን የእግዚአብሔር በጎ ፈቃድ ሆኖአልና።
22 መቼም አይሁድ ምልክትን ይለምናሉ የግሪክ ሰዎችም ጥበብን ይሻሉ፥
23 እኛ ግን የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን፤ ይህም ለአይሁድ ማሰናከያ ለአሕዛብም ሞኝነት ነው፥
24 ለተጠሩት ግን፥ አይሁድ ቢሆኑ የግሪክ ሰዎችም ቢሆኑ፥ የእግዚአብሔር ኃይልና የእግዚአብሔር ጥበብ የሆነው ክርስቶስ ነው።
25 ከሰው ይልቅ የእግዚአብሔር ሞኝነት ይጠበባልና፥ የእግዚአብሔርም ድካም ከሰው ይልቅ ይበረታልና።
26 ወንድሞች ሆይ፥ መጠራታችሁን ተመልከቱ፤ እንደ ሰው ጥበብ ጥበበኞች የሆኑ ብዙዎች፥ ኀያላን የሆኑ ብዙዎች፥ ባላባቶች የሆኑ ብዙዎች አልተጠሩም።
27 ነገር ግን እግዚአብሔር ጥበበኞችን እንዲያሳፍር የዓለምን ሞኝ ነገር መረጠ፤ ብርቱንም ነገር እንዲያሳፍር እግዚአብሔር የዓለምን ደካማ ነገር መረጠ፤
28 እግዚአብሔርም የሆነውን ነገር እንዲያጠፋ የዓለምን ምናምንቴ ነገር የተናቀውንም ነገር ያልሆነውንም ነገር መረጠ፥
29 ሥጋን የለበሰ ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት እንዳይመካ።
30 -
31 ነገር ግን። የሚመካ በእግዚአብሔር ይመካ ተብሎ እንደ ተጻፈው ይሆን ዘንድ፥ ከእግዚአብሔር ዘንድ ጥበብና ጽድቅ ቅድስናም ቤዛነትም በተደረገልን በክርስቶስ ኢየሱስ የሆናችሁ ከእርሱ ነው።

በመጀመርያ ጥበብን በሁለት ከፍለን እንድናይ ግድ ይለናል፣ የዓለም ጥበብና የእግዚአብሔር ጥበብ።

በአጭሩ ስንገልገልጻቸው፡

·         የዓለም ጥበብ ጊዜያዊ ነው

·         የእግዚአብሔር ጥበብ ዘላለማዊ ነው

ብዙ ጊዜ ጥበብ ሲነሳ በመጀመርያ የሚታወሰን ጠቢቡ ሰለሞን  ነው ብዬ እገምታለሁ።

ታሪኩም በ1 ነገስት 3 እና 4 ላይ ይገኛል።

የሰለሞን ጥበብ በዋናነት ምድራዊ የነበረና የዓለምን ታላላቅ መንግስታት ቀልብ የሳበ ነበር። የጥበቡም ታላቅነት የሚወዳደረው በዘመኑ ከነበሩ የምስራቅ ሰዎችና ከግብጽ ጋር ነበር። ከነሱም ተወዳድሮ ወደር አልተገኘለትን ነበር። ነገር ግን የሰለሞንን ታሪክ ስናጠናው በእድሜው መገባደጃ ላይ ልቡ ከእግዚአብሄር እንደራቀና እግዚአብሄር እንዳዘነበት በመጨረሻም እንደሞተ እናያለን።

ዛሬ ግን የማተኩረው ከሰለሞን የሚበልጠው በሚል ሉቃስ 11፡31 በተገለጸው ላይ ነው።

የሰለሞን ጥበብ ሲያልፍና ሲረሳ የእርሱ ግን ዘላለማዊ የሆነና ተወዳዳሪ የሌለው ነው።

እስቲ ወደ ዋናው መልእክቴ ከመግባቴ በፊት

ጥበብ ምንድን ነው ወዴትስ ይገኛል የሚለውን ከመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ባጭሩ እንይ



ጥበብ ምንድን ነው

ምሳሌ 4፡7 ጥበብ ታላቅ ነገር ናት፤ ስለዚህ ጥበብን አግኛት፤ያለህን ሁሉ ወይም ያገኘኸውን ሁሉ ብታስከፍልህም ማስተዋልን ገንዘብህ አድርጋት።

 ምሳሌ 3፡13-14 ጥበብን የሚያገኛት፣ ማስተዋልንም ገንዘቡ የሚያደርጋት ሰው ቡሩክ ነው፤ እርሷ ከብር ይልቅ ትርፍ የምታመጣ፣ ከወርቅም ይልቅ ጥቅም የምታስገኝ ናትና።

 ምሳሌ 16፡16 ከወርቅ ይልቅ ጥበብን ማግኘት፣ ከብርም ማስተዋልን መምረጥ ምንኛ ይበልጣል!

 ምሳሌ 8፡1 - 6 ጥበብ ጮኻ አትጣራምን? ማስተዋልስ ድምፅዋን ከፍ አድርጋ አታሰማምን? በመንገድ አጠገብ ባሉ ኰረብቶች፣ መንገዶቹ በሚገናኙበትም ላይ ትቆማለች፤ወደ ከተማዪቱ በሚያስገቡት በሮች አጠገብ፣ በመግቢያዎቹ ላይ፣ ድምጿን ከፍ አድርጋ እንዲህ ስትል ትጮኻለች፤

“ሰዎች ሆይ፤ የምጠራውኮ እናንተን ነው፤ ለሰው ልጆች ሁሉ ድምፄን ከፍ አደርጋለሁ።

እናንተ ብስለት የጐደላችሁ፤ ጠንቃቃነትን ገንዘብ አድርጉ፤እናንተ ተላሎች፤ ማስተዋልን አትርፉ። የምናገረው ጠቃሚ ነገር ስላለኝ አድምጡኝ፤ ቀና ነገር ለመናገር ከንፈሮቼን እከፍታለሁ።

 ምሳሌ 3:13 ጥበብን የሚያገኛት፣ ማስተዋልንም ገንዘቡ የሚያደርጋት ሰው ቡሩክ ነው፤

 ምሳሌ 4:5 ጥበብን አግኛት፤ ማስተዋልን ያዛት፤ ቃሌን አትርሳ፤ ከእርሷም ዘወር አትበል።

ጥበብ ወዴትስ ይገኛል   

ምሳሌ 15፡33 እግዚአብሔርን መፍራት ጥበብን መማር ነው፤ወይም ጥበብ እግዚአብሔርን መፍራት ታስተምራለች።ትሕትናም ክብርን ትቀድማለች።

ምሳሌ 19:23 እግዚአብሔርን መፍራት ወደ ሕይወት ይመራል፤እንዲህ ያለውም ሰው እፎይ ብሎ ያርፋል፤ መከራም አያገኘውም።

ምሳሌ 23:17 – 18 ልብህ በኀጢአተኞች አይቅና፤ነገር ግን ዘወትር እግዚአብሔርን ለመፍራት ትጋ። ለነገ ርግጠኛ አለኝታ ይኖርሃል፤ ተስፋህም ከንቱ አይሆንም።

ምሳሌ 28:14 እግዚአብሔርን ዘወትር የሚፈራ ሰው ቡሩክ ነው፤ ልቡን የሚያደነድን ግን መከራ ላይ ይወድቃል።

የእግዚአብሔር ፈቃድ

ዳዊት

መዝሙር 40፡8 አምላኬ ሆይ፤ ፈቃድህን ላደርግ እሻለሁ፤ ሕግህም በልቤ ውስጥ አለ።

መዝሙር 143፡10 አንት አምላኬ ነህና ፈቃድህን ለማድረግ አስተምረኝ፤ ቅዱስ መንፈስህም በጽድቅ ምድር ይምራኝ።

ሓዋ 13:36 “ዳዊት በራሱ ዘመን የእግዚአብሔርን ፈቃድ ካገለገለ በኋላ አንቀላፍቶአል፤ …”

ጳውሎስ

1 ቆሮንቶስ 1፡1 በእግዚአብሔር ፈቃድ የክርስቶስ ኢየሱስ ሐዋርያ እንዲሆን ከተጠራው ከጳውሎስ፣ 

ሓዋ 21፡14 ምክራችንን አልቀበል ስላለን፣ “እንግዲህ የጌታ ፈቃድ ይሁን” ብለን ተውነው።

ሮሜ 8፡5 እንደ ሥጋ የሚኖሩ ልባቸውን በሥጋ ፍላጎት ላይ ያሳርፋሉ፤ እንደ መንፈስ የሚኖሩ ግን ልባቸውን በመንፈስ ፍላጎት ላይ ያደርጋሉ።

ሮሜ 12፡2 መልካም፣ ደስ የሚያሰኝና ፍጹም የሆነውን የእግዚአብሔር ፈቃድ ምን እንደሆነ ፈትናችሁ ታውቁ ዘንድ በአእምሮአችሁ መታደስ ተለወጡ እንጂ ይህን ዓለም አትምሰሉ።

ክርስቶስ

ማቴዎስ 6፡10 መንግሥትህ ትምጣ፤ ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች፣ እንዲሁ በምድር ትሁን።

ኢሳያስ 53፡10 መድቀቁና መሠቃየቱ ግን የእግዚአብሔር ፈቃድ ነበር፤ እግዚአብሔር ነፍሱን የኀጢአት መሥዋዕት ቢያደርገውም እንኳ፣ ዘሩን ያያል፤ ዕድሜውም ይረዝማል፤ የእግዚአብሔርም ፈቃድ በእጁ ይከናወናል።

ሉቃስ22፡42 እንዲህም አለ፤ “አባት ሆይ፤ ፈቃድህ ከሆነ፣ ይህችን ጽዋ ከእኔ ውሰድ፤ ነገር ግን የእኔ ፈቃድ ሳይሆን የአንተ ፈቃድ ይፈጸም።”

ዪሓንስ4፡34 ኢየሱስም እንዲህ አላቸው፤ “የእኔ ምግብ የላከኝን ፈቃድ ማድረግና ሥራውን መፈጸም ነው፤ 

ዪሓንስ6፡38 ከሰማይ የወረድሁት የራሴን ፈቃድ ለማድረግ ሳይሆን፣ የላከኝን የእርሱን ፈቃድ ለመፈጸም ነውና፤ 

ማቴዎስ 12፡49-50 በእጁም ወደ ደቀ መዛሙርቱ እያመለከተ እንዲህ አለ፤ “እናቴና ወንድሞቼ እነዚህ ናቸው፤ በሰማይ ያለውን የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ ሁሉ፣ ወንድሜ፣ እኅቴና እናቴም ነው።

ጥበበ እና የእግዚአብሔር ፈቃድ

ምሳሌ 19:21 በሰው ልብ ብዙ ሐሳብ አለ፤ የሚፈጸመው ግን የእግዚአብሔር ሐሳብ ነው።

ምሳሌ 21:30 እግዚአብሔርን ለመቋቋም የሚያስችል፣ አንዳችም ጥበብ ማስተዋልና ዕቅድ የለም።

መክብብ2:25 ከእርሱ ዘንድ ካልሆነ ማን መብላትና መደሰት ይችላል?

(ያለ እርሱ ፈቃድ የበላ ደስ ብሎትም ተድላን የቀመሰ ማነው?

ማቴዎስ 7፡21 “በሰማይ ያለውን ያባቴን ፈቃድ ሳይፈጽምጌታ ሆይ፤ ጌታ ሆይ፤የሚለኝ ሁሉ ወደ መንግሥተ ሰማይ አይገባም።

እንግዲህ ጥበብ እንደ ሌላቸው ሳይሆን እንደ ጥበበኞች እንዴት እንደምትኖሩ ተጠንቀቁ። ቀኖቹ ክፉ ናቸውና ዘመኑን በሚገባ ዋጁ። ስለዚህ ሞኞች አትሁኑ፤ የጌታ ፈቃድ ምን እንደሆነ አስተውሉ እንጂ።

ኤፌሶን 5: 15 – 17

ከእናንተ ማንም ጥበብ ቢጎድለው፣ ሳይነቅፍ በልግስና ለሁሉም የሚሰጠውን እግዚአብሔርን ይለምን፤ ለእርሱም ይሰጠዋል

ያዕቆብ 1:5


በእ/ር ቃል መቃኘት

 

“እርሱ ኋጢአትን ሊያስወግድ እንደተገለጠ ታውቃላችሁ፤ በእርሱም ኋጢአት የለም። በእርሱ የሚኖር ኋጢአትን  አያደርግም፤ ኋጢአትን  የሚያደርግ ግን እርሱን አላየውም ወይም  አላወቀውም። ልጆች ሆይ፤ ማንም እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ፤ እርሱ ጻድቅ እንደሆነ ጽድቅን የሚያደርግ ጻድቅ ነው። ኋጢአትን የሚያደርግ ከዲያቢሎስ ነው። ምክንያቱም ዲያቢሎስ ከመጀመርያው አንስቶ ኋጢአትን የሚያደርግ ነው። የእግዚአብሔር ልጅ የተገለጠውም የዲያቢሎስን ስራ ሊያፈርስ ነው። ከእግዚአብሔር የተወለደ ሁሉ ኋጢአትን አያደርግም፤ የእርሱ ዘር በውስጡ ይኖራልና፤ ከእግዚአብሔር የተወለደ ኋጢአትን ሊያደርግ አይችልም። የእግዚአብሔር ልጆችና የዲያቢሎስ ልጆች ተለይተው የሚታወቁት በዚህ ነው፤ ጽድቅን የማያደርግ፣ ወንድሙንም የማይወድ ሁሉ ከእግዚአብሔር አይደለም።”  1 ዮሐንስ 3 ፡ 5—10

የነዚህን አምስት ቁጥሮች በአጥጋቢ መልኩ ለመረዳት በጠቅላላ የዮሐንስ መልዕክትን ማወቅ ግድ ስለሚል፣ የዮሐንስን መልዕክት በአጭሩ እንከልሰውና፣ በዚህ ዘመን ከዚህ መልዕክት ምን እንማራለን የሚለውን አይተን እንጨርሳለን።

ሐዋርያው ዮሐንስ በጥንቷ ኤፌሶን ተቀምጦ ሳለ ሐዋርያዊ ሃላፊነት ተቀብሎባቸው ለነበሩ በአጎራባች ከተሞች ላሉ በርከት ያሉ የቤት ለቤት ቤተክርስቲያኖችን የተጻፈ ተጓዥ  መልዕክት ነው ለዚህ ነው በአንደኛ መልዕክቱ ላይ ለማን እንደተጻፈ ያልተገለጠበት ምክንያት።


በመልዕክቶቹ ላይ እንደምንረዳው የተጻፈላቸው አማኞች ለሆኑ አይሁዶች የነበረ ሲሆን፣ የተጻፈበት ዋና ምክንያትም በዛ ወቅት በነበረው የሃሰት ትምህርት እንዳይናወጡ ነው።

ይህ የሃሰት ትምህርትም የተነሳው በተወሰኑ ቤተክርስቲያናቱን ጥለው በወጡ ስብስቦች ሲሆን፣ እነርሱም

·    የክርስቶስን መሲህነት የማይቀበሉ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን የሚክዱና ይህን የሃሰት ትምህርትንም አንቀበልም ብለው በቤተክርስታያናቸው የቀሩትን ሰዎች እንደ አላዋቂዎችና ለእውነት ጠላቶች አድርገው ይቆጥሩ ስለነበር ነው።

እነዚህ የሃሰት አስተማሪዎች ወይም ሐዋርያው ዮሐንስ “አሳቾች”የሚላቸው፣ የሚያስተምሩት ከኋጢአትና ከዓለም መለየት ድነትን ለሚያስገኝ እምነት አስፈላጊ አይደሉም በማለት  ስለነበር ነው።

ይህንንም ዓይነት ትምህርት በማስተማር ከሥነ—ምግባር ውጭ የሆነ ኋጢአትን የማይጠየፍ የኑሮ ልምምድ ይከተሉ የነበሩ ሲሆን፣

ለዚህ ነው ዮሐንስ

“በእርሱ የሚኖር ኋጢአትን  አያደርግም፤ ኋጢአትን  የሚያደርግ ግን እርሱን አላየውም ወይም  አላወቀውም። ልጆች ሆይ፤ ማንም እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ፤ እርሱ ጻድቅ እንደሆነ ጽድቅን የሚያደርግ ጻድቅ ነው። ኋጢአትን የሚያደርግ ከዲያቢሎስ ነው።” ብሎ የፃፈው።

ወደዚህ ዓይነት አኗኗር ያስገባቸው ትልቁ ስህተትና የትምህርታቸው ዋና መሰረት የሆነው፣ መንፈስ በጠቅላላው ጥሩ ሲሆን፣ ቁስ ወይም ስጋ ደግሞ ሰይጣናዊ ነው የሚለው Gnosticism የተባለው አስየምህሯቸው ነው።

የዚህ አስተምህሮ ከዋናዎቹ መሰረታዊ ስህተቶቹ ጥቂቶቹ፡

1.      ቁስ ስለሆነ ሰዎች ስጋ ሳይሆኑ መንፈስ ናቸው፣ ምክንያቱም ቁስ ከሰይጣን ነው፣ መንፈስ ብቻ ነው ከእ/ር የሆነው

2.     ክርስቶስ በስጋ አልተገለጠም ወይም ሥጋ የሚመስል ነገር ነበር ያለው እንጂ ስጋ ለብሶ አልተመላለሰም

3.     የክርስቶስ አምላካዊ ባህርይ በምድር የተገለጠው ክርስቶስ ሲጠመቅ እንጂ ሰውም አምላክም ሆኖ አልመጣም፣ ደግሞም ሲጠመቅ የተገለጠው አምላካዊ ባህርይ ሲሞት ተለይቶታል።

4.     ስጋ ከሰይጣን ስለሆነና ቁስ ብቻ ስለሆነ በስጋችን የእ/ርን ሕግ ብንጥስም ምንም አይነት ችግር አያመጣም፣ ምክንያቱም መንፈሳችን ብቻ ነው ደህንነት ያገኘው የሚሉት ናቸው

ዚህ ዮሐንስ በዚያ ዘመን (1 ና 2ኛ ክ/ዘመን) ላይ ለነበሩ እውነተኛውን ወንጌል የተቀበሉት ሰዎች በነዚህ የሃሰት ትምህርቶች እንዳይናወጡ ነው ይህን መልዕክት የሚጽፍላቸው።

ይህ መልዕክት ከደብዳቤነቱ ይልቅ ግጥማዊ ቃና ያለው ለየት ባለ የአፃፃፍ ዘይቤ “Amplification” የተባለውን ዓይነት በስዕላዊ መግለጫና ዋናውን የወንጌልን ሃሳብ

·         ይወትን፣ እውነትንና ፍቅርን

በተደጋጋሚ በተለያዩ አንግሎች በማንሳትና፤

·         ውነትን ከውሸት፣

·         ፍቅርን ከጥላቻ፣

·         ብርሃንን ከጨለማ፣

·         የእ/ር ልጅነትን ከዲያቢሎስ ልጅነት

ንጽጽር እያስቀመጠ ከዚህ በፊት ያስተማራቸውን የወንጌል ትምህርት በድጋሚ የሚያብራራበት ክፍል ነው።

ቅድም ያነበብነው ክፍል ላይም

“የእግዚአብሔር ልጆችና የዲያቢሎስ ልጆች ተለይተው የሚታወቁት በዚህ ነው፤ ጽድቅን የማያደርግ፣ ወንድሙንም የማይወድ ሁሉ ከእግዚአብሔር አይደለም።” ይላል።

ጠቅልል አድርገን ስናየው ይህ የዮሐንስ መልዕክት ጠንካራ መግቢያ Introduction 1:1-4 ያለው ሲሆን

“ስለ ሕይወት ቃል ከመጀመርያ የነበረውን፣የሰማነውን፣ በዓይኖቻችን ያየነውንና እጆቻችን የዳሰሱትን እንናገራለን።” ብሎ በጠንካራ መግቢያ ይጀምራል

ዩሐንስ ምን እያላቸው ነው፣ ከክርስቶስ ከራሱ የተማርነውን ፣ ክርስቶስን በስማ በለው አይደለም የምናውቀው፣ ሕያው ምስክሮች ነን።

በመደምደምያው Conclusion ላይ ደግሞ 5፡18—21 እርግጠኝነት በተላበሰ አባባል ተመሳሳይ ነገር ይናገራ።

“የእግዚአብሔር ልጅ እንደመጣ፣ እውነተኛ የሆነውን እርሱን እርሱን እንድናውቅ ማስተዋልን እንደሰጠን እናውቃለን፤ እኛም እውነተኛው በሆነው በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ አለን።  እርሱ እውነተኛ አምላክና የዘላለም ሕይወት ነው።”

በመግቢያውና በመደምደምያው መሃከል ደግሞ ለሁለት ከፍሎ ሰፋ ያለ ማብራርያ ይሰጠናል።

በመጀመርያው ክፍል 1፡5 — 3፡10 ስለ ብርሃን የሚገልጽበት ሲሆን

ሁለተኛው ክፍል 3፡11—5፡17  ደግሞ ስለ ፍቅር የሚገልጽበት ነው።

በሁለቱም ክፍሎች መግቢያ

1፡5 ከእርሱ የሰማነውን ለእናንተም የምንነግራችሁ መልዕክት 

3፡11 ከመጀመርያ የሰማችኋት . . . . . . ይህች ናት this is the message

ባጭሩ ዮሐንስ በመጀመርያው ክፍል ላይ በብርሃን መመላለስ ማለት ከእ/ር ጋር ህብረት ማድረግ ማለት ነው ይላል። ህብረት የሚለው ቃል በተለይ እዚህ ጋር ትርጉሙ ጥምረት፣ ተካፋይ መሆን፣ ተሳታፊ መሆን ማለት ነው። ከእ/ር ጋር ያጣመረን፣ ተካፋዮች የሆነው ደግሞ በልጁ በክርስቶስ በኩል ነው የለናል።

ከእ/ር ጋር ህብረት አለን ስንል ደግሞ በብርሃን እንመላለለን ማለት ነው። በብርሃን መመላለስ ማለት ደግሞ ትዕዛዙን እንጠብቃለን ማለት ነው። ይህ ማለት እ/ርን በፍጹም ልባችን፣ በፍጹም ነፍሳችን፣ በፍጹም ሃሳባችን መውደድ ማለት ሲሆን፣ ነገር ግን ትዕዛዛቱን ሁሉ መጠበቅ ከባድ ቢሆንም ነገር ግን ብትወድቁ ከኋጥያት የሚያነጻችሁ የክርቶስ ደም አለ ብሎ      1፡5—10 ያገልጽላቸዋል።

በብርሃን መመላለስ ደግሞ ማለት እርስ በእርስ ህብረት መፍጠርም ጭምር ነው ብሎም ይገልጸዋል።

ደግሞም በብርሃን ከተመላለሳችሁ በዚህ አለም ላይ ድል ትቀዳጃላችሁ በዚህም ኋጥያትን እንዳትሰሩ ትጠበቃላችሁ የሚልም መልዕክ ያስተላልፍላችዋል።

በሁለተኛውም ክፍል 3፡11 — 5 ፡17

እ/ር ፍቅር ነው እናም የእ/ር የሆኑት እርስ በእርስ ይዋደዳሉ፣ ስለዚህ ጥላቻ በእናንተ ዘንድ አይኑር ይላቸዋል። ይህንንም የተማርነው ከአንዱ ከእ/ር ልጅ ከክርስቶስ ነው፣ እርሱም ስለእኛ ነፍሱን አሳልፎ እስኪሰጠን ድረስ አለም ወዷልና። ስለዚህ ክርስቶስ ያስተማረን ባልንጀራህን ውደድ የሚል ነው። ለዚህም ነው ባነበብነው ክፍል ላይም “ወንድሙንም የማይወድ ሁሉ ከእግዚአብሔር አይደለም።”

ስለዚህ መናፍስትን መርምሩ ምክንያቱም ብዙ ሃሰተኛ ነቢያት ወደ ዓለም መጥተዋልና። እነዚህንም ሃሰታኛ ነብያት የምትለዩዋቸው በትምህርታቸው ነው። ብሎ በም 4 ላይ ይናገራል።

እነርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ አልተገለጠም ብለው የሚያስተምሩና የዓለምን ስርዓት የሚከተሉ ናችው፣ የሚናገሩትም እንደ ዓለም ነው፣ ዓለምም ይሰማቸዋል። ስለዚህ ዓለም እናንተን ባይሰማችሁ አይግረማችሁ እናንተ ከዓለም ስላይደላችሁ ነው።

በ2፡16 —17 “በዓለም ያለው ሁሉ፥ የስጋ ምኞት፣ ያዓይን አምሮት የኑሮ ትምክህት ከዓለም የሚመጣ እንጂ ከእ/ር አይደለም። ዓለምና ምኞቱ ያልፋሉ፤ የእ/ርን ፈቃድ የሚፈጽም ግን ለዘላለም ይኖራል።”  ይላል።

ሐዋርያው ደጋግሞ የምጽፍላችሁ የመጀመርያውን የቆየውን ትዕዛዝ እንጂ ሌላ አዲስ ትዕዛዝ አይደለም እያለ ይነግራቸዋል። ይህም ማለት በመጀመርያ ከክርስቶስ የተማርነውንና ያየነውን የነገርናችሁን አሁንም አጥብቃችሁ ያዙ እያላቸው ነው።

ይህች በመጀመርያ ከክርስቶስ የሰሟት ትዕዛዝ በማቴዎስ ወንጌል 22፡35 — 40 ላይ ያለው

“ከእነርሱም አንድ የኦሪት ሕግ አዋቂ ሊፈትነው ፈልጎ እንዲህ አለው።

መምህር ሆይ ከህግ ሁሉ የሚበልጠው የትኛው ትዕዛዝ ነው?

እርሱም እንዲህ አለው፤ “ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስህ በፍጹም ሃሳብህ ውደድ”፣ ይህ የመጀመርያው ከሁሉ የሚበልጠው ትዕዛዝ ነው፤

ሁለተኛውም ያንኑ ይመስላል ይህም “ጎረቤትህን እንደራስህ  ውደድ” የሚለው ነው፤ ሕግና ነቢያት በሙሉ በእነዚህ ሁለት ትዕዛዛት ላይ የተንጠለጠሉ ናቸው።”

አሁንም ዮሃንስ መልሶ የሚያስተምራቸው ይህንኑ ትዕዛዝ ነው።

እኛም በዚህ ዘመን ሃሰተኞች ነብያትን የምንለየው በዚሁ መንገድ ነው። የቀደመውን ትዕዛዝ በመፈጸም። ያንንም የምናገኘው በእ/ር ቃል ውስጥ ነው።

በአሜሪካ ውስጥ ሃሰተኛ የዶላር ኖቶችን የሚይዙ ሰዎች የሚሰለጥኝት እንዴት እንደሆነ ታውቃላችሁ?

ሃሰተኛ የዶላር ኖቶችን ሰብስቦ በማጥናት አይደለን፣ ይልቁንም እውነተኛውን የዶላር ኖት በደንብ በማጥናት እንጂ። እውነተኛውን በደንብ ጠንውቀው ሰለሚያውቁት ሃሰተኛውን በቀላሉ ይለዩታል።

እኛም የእ/ር ቃል ጠንቅቀን ካወቅን ሃሰተኛ ትምህርቶችን ለይተን ማወቅ እንችላለን። ዳዊት ከዚህ ነው “ሕግህ ለእግሬ መብራት ለመንገዴ ብርሃን ነው የሚለው”

የመጀመርያው ሃሰተኛ አስተማሪዎችን የምንለይበት መንገድ ትምህርታቸው ክርስቶስ ማዕከል ያላደረገ እንደሆነ ነው። ለዚህ ነው 4፡3 ኢየሱስን የማይቀበል መንፈስ ግን ከእ/ር አይደለም።

ብዙ ጊዜ ሃሰተኛ አስተማሪዎች ስለራሳቸው ነው የሚያወሩት፣ እነርሱ እንዴት ልዩ እንደሆኑና በእ/ር እንደተመረጡ። እ/ር እነርሱን ብቻ እንደሚናገራቸው፣ እነርሱ ብቻ እንዲታዮ ነው የሚፈልጉት።

ሌላው ዓለማዊ ነገር ላይ፣ የሚያልፍ ነገር ላይ ትኩረት ይሰጣሉ፣ ሃብት ጤና ምቾት። እ/ር ልጁን የላከው እኛ በሚያልፈው ዓለም ላይ ተመችቶን እንድንኖር ሳይሆን ዘላለምን በመንግሰት ሰማያት ከአባታችን ጋር እንድንኖር ነው። ትንቢታቸውም ትምህርታቸውም ትበለጽጊያለሽ ይሳካልሻል ብቻ ነው።

ጽድቅን ብዙ ጊዜ አይሰብኩም፣ ከነርሱ ትምህርት ጋር የማይስማማውንም ልክ እውነትን እንደሳት እንዳልገባው ኋላ እንደቀረ አድርገው ያንቋሽሻሉ።

በመጨረሻም ዮሐንስ የመጀመርያውን መልዕክቱን የደመደመው

“ልጆች ሆይ ራሳችሁን ከጣዖቶች ጠብቁ” ነው ያለው።

ምን ማለቱ ነው ራሳችሁን ከማንኛውም ታላቁን እ/ርን ከራሱ ዕውቀት ብቻ ተነስቶ የእ/ርን ማንነት ለማናገር ከሚያስደፍር ሙከራ አርቁ ማለቱ ነው።

በዚህ ዘመን ያለው ጣዖት ራስን አግዝፎ የማየት፣ የዕውቀት ሁሉ ምንጭ ማድረግ፣ ከዚህም የተነሳ ልክ ዓለም ውስጥ እንዳሉ ሰዎች ሁሉ ለመታወቅ መጣር ነው።

ክርስቶስን ማወቅ ማለት እ/ርን ማወቅና ሌሎችን እንደራስ ማየትና ለሌሎች መኖር ማለት ብቻና ብቻ እንደሆነ ተገንዘቡ።

የሚመጣው ዓመት የሁሉ መሰረት በሆነው በእ/ር ቃል የመቃኘት ዓመት እንዲሆንልን ምኞቴና ፀሎቴ ነው።

Wednesday, April 8, 2020

በዚህ ጊዜ ምን እናድርግ?

ከብዙ ዝምታ በኋላ ይህን ጽሁፍ ለመጻፍ የተነሳሁት ጥልቅ የሆነውን የዓለም ጉዳይ የተረዳን ስላልመሰለኝ ነው። በተለይም የኮሮና ቫይረስ ክትባት አፍሪካ ውስጥ ይሞከር የሚለው ጉዳይ ሳይታሰብ አፈትልኮ ሲወጣ አሁን ዝምታው ይብቃኝ ብዬ ነው።

በመጀመርያ ኮሮና ቫይረስ ምንድን ነው? የሚለውን ባጭሩ ላብራራ። ኮሮና እንደ ማንኛውም ቫይረስ፣ ቫይረስ ነው። ቫይረስ ማለት ደግሞ ከተክልም፣ ከእንስሳትም ሆነ ከባክቴርያ ዘር ውጭ የሆነ፣ ሕይወት ካላቸው ነገሮች ጋር የማይመደብ ከሚኖርበት ሕይወት ያለው ነገር ውጭ ሕይወት የለሽ የሆነ በአይን የማይታይ “ነገር” ነው። በተራቀቀው የማይክሮ ባዮሎጂ (Microbiology) አገላለጽ ቫይረስ ማለት የኒኩሊክ  አሲድ(Nucleic acid)፣ የዘረ መል (DNA) ወይም የቅድመ ዘረመል (RNA) እና የፕሮቲን (protein) ቅንብር ሲሆን፤ መኖርያ የሚሆነው ሕዋስ ሲያገኝ ውስጡ ባለው በኑክሊክ አሲድ አማካኝነት አዳዲስ የዘረ መል ቅንብር ያላቸው ሌሎች ቫይረሶችን ማባዛት ይጀምርና እነዚህም የተባዙት ቫይሪኦን (Virion) የተሰኙ ኢንፌክሽን የማሰከተል አቅም ያላቸው ተውሃሶች፣ የሚኖሩበትን ሕዋስ በፍጥነት ይወሩታል። ቫይረሶች በአጠቃላይ ያለ ሕዋስ (አትክልት፣ ሰው፣ እንስሳ) ረጅም ዕድሜ የላቸውም፣ እንዲሁም በራሳቸው የሚያስከትሉት ጉዳትም እምብዛም የሌለ ሲሆን ይልቁንም ቫይረሱ የሚኖርበት ሕዋስ የቫይረሱን ወረራ ለመከላከል በሚያደርገው ትንቅንቅ (immune response) የተለያዩ የህመም ምልክቶችን ማየት እንጀምራለን፤ ለምሳሌ በዋነኝነት ትኩሳት። በዚህ መልኩ ሰውነታች በራሱ የመከላከል እርምጃ የቫይረሱን መራባት ይገታውና ከከፋ ኢንፌክሽን ያድነናል።

ወደ ኮሮና ስንመጣ ኮቪድ—19 የተባለው ቫይረስም እንዲሁ እንደሌሎቹ ቫይረሶች የራሱ የሆነ ሕይወት የሌለው “ነገር” ነው። ነገር ግን አዲስና ከዚህ በፊት ከነበሩት የቫይረስ ዓይነቶች የሚለይበት የራሱ የሆነ መለያ ያለውና እስካሁን የሰው ልጆች ከጋጠማቸው ቫይረሶች የተለየ ስለሆነ፣ የሰውነታችን የመከላከያ ስርዓት እምብዛም ስለማያውቀው፣ ሰውነታችን የመዋጋት አቅሙን ጨምሮ የራሱን የሰውነት ክፍሎች የሚጎዳበት ሁኔታ ይፈጠርና፣ በተለይም ኮቪድ—19 የሚያጠቃው የመተንፈሻ አካላትን ስለሆነ፣ ከሳምባ ጋር ተያይዞ የመተንፈስ አቅምን ሲያሳጥርና የተለመደውን የኦክሲጅን ኡደት ሲዛባ ወደ ከፋ አደጋ ይሻገራል። ይህ ቫይረስ አዲስና ባልተለመደ መልኩ የተለያዩ ቁሶች ላይ በሕይወት የመቆየት አቅሙ ከፍተኛ ስለሆነ፣ በቤተ ሙከራ ውስጥ የተፈጠረ ቫይረስ ሊሆን እንደሚችል መጠርጠር ያስችላል። የግሌ መላምትም ይህ ቫይረስ በተለይ ብረት ነክ ነገሮች ላይ በሕይወት የመቆየት አቅሙ ከፍተኛ መሆኑንና በአየር ላይ እስከ 8 ሜትር የመንሳፈፍ ባህሪው ሰው ሰራሽ ቫይረስ ይሆናል የሚል ነው።

ስለዚህ ምን እናድርግ? የውን ከመመለሳችን በፊት ቫይረስ ምን እንደሆነና የኮሮናን ባህርይ ደግሞ ማየታችን የሚጠቅመን፣ ከዚህ ወረርሽኝ ኢትዮጵያን ከከፋ አደጋ ለማዳን ምን ማድረግ ይቻል ነበር የሚለውንና፣ አሁንስ ምን እናድርግ የሚሉትን ጥያቄዎች ለመመለስ ነው።

እንደኔ ሃሳብ ምንም እንኳን የዘገየ አስተያየት ቢሆንም፣ እንደ አገር ማድረግ የነበረብን የመንገደኞች አየር በረራዎችን ከአንድ እስከ ሦስት ወር ድረስ መዝጋት ይገባን ነበር ብዬ አስባለሁ። የአየር መንገዱንም አሁን ለኮረና መከላከያ ተብሎ የተሰበሰበው ገንዘብ በድጎማ መልክ በመስጠት ኪሳራውን መሸፈን ይሻል ነበር የሚል አቋም ነው ያለኝ። በሌላ አማራጭም በረራዎችን መዝጋት ኢኮኖሚው ላይ ከባድ አደጋ አለው ከተባለ፣ አሁንም ቀላሉ እና አዋጩ መንገድ ይሆን የነበረው በጣም ዘግይቶ የተጀመረው ወደ አገር የሚገቡ መንገደኞችን ለይቶ ለ14 ቀናት መከታተል ቀደም ብሎ ቢጀመር ነበር። ነገር ግን እነዚህ ሁለት ነገሮች በጊዜው አልተተገበሩም።

አሁንም እስኪ ተመልሰን ስለ ቫይረሱ እናንሳ። ከላይ እንዳልነው ቫይረስ የራሱ የሆነ ሕይወት የሌለው “ነገር” ነው፣ ስለዚህ አገራችን የሌለን ቫይረስ በእርግጥም ይዞ የሚመጣው ቫይረሱ ካለበት ቦታ የመጣ ሰው ብቻ ነው።

አሁን ታድያ ምን እናድርግ? እንደ አገር ዋነኛ ማድረግ ያለብን ነገር ሙሉ ለሙሉ የሰዎችን እንቅስቃሴ ማቆም ብቻ ነው። ይህ እርምጃ ለእኛ ዓይነቱ ደሃ አገር አዋጭ አይደለም የሚሉ ሃሳቦች ይነሳሉ። አሁንም በአጽንኦት የምመክረው ነገር፣ የዕለት ጉርሻውን እያሳደደ የሚኖረው ምን ይሁን፣ ጎዳና ተዳዳሪዎችስ፣ የሥርዓተ አልበኝነቱስ ነገር እና የመሳሰሉት ጥያቄዎች ሊነሱ ይችላሉ። አንድ ነገር ግን ማየት ያልቻልነው እነዚህ ሰዎች በረሃብ ያልቃሉ ብለን ነው የፈራነው እንጂ እንቅስቃሴዎችን ባለመግታታችን በበሽታ ማለቃቸውን አናስቀረውም። መንግስት እስካሁን የወሰዳቸው እርምጃዎች ያላዋቂ ሳሚ ዓይነት ሆነውብኛል። ለተወሰነ ጊዜ እንቅስቃሴ ማገድ ስንል ምን ማለት እንደሆነ የፖለቲካ ሹመኞቹ የገባቸው አይመስሉም። የሰዎች እንቅስቃሴ ሲቆም የቫይረሱም እንቅስቃሴ ይቆማል፣ ቫይረሱ ባለበት ሲቆይ ደግሞ ይሞታል። ቫይረሱ የያዛቸው ሰዎች ደግሞ ግፋ ቢል ጥቂት ሰዎች ላይ ብቻ አስተላልፈው የበሽታው ምልክት ይታይባቸውና፣ እነርሱም ሆኑ ከእነርሱ ጋር የተነካኩ ሰዎች ተለይተው ጥብቅ ሕክምና ይደረግላቸዋል፣ በዚህም ቫይረሱን እኛን ከመቆጣጠሩ በፊት እኛ እንቆጣጠረዋለን።

ከዚህ ክስተት ምን እንማር? ከዚህ ክስተት እምናየው ድህነታችን የኢኮኖሚ ብቻ አለመሆኑን፣ ይልቅም የአስተሳሰብ መሆኑን ነው። አሁን ዞር ብለን እስከዛሬ የኖርንበትን የአኗኗር ዘይቤ የምናስተውልበት ጊዜ መሆን ይገባዋል። እስከዛሬ ፖለቲካ አገሪቷን ሲመራ ነበር፣ የኛው ፖለቲካ ደግሞ የሚመራው በጥቅመኛና አስመሳይ ሰዎች እንጂ በዕውቀት አይደለም። ዛሬ ላይ ቆመን ችግሩን እያየን መድሐኒት አገኘን እያልን የምንዘባበትበት ጊዜ የለንም፣ እስከዛሬ በሰላሙ ጊዜ እንስራ የሚሉ ሰዎች የሚገፉበትን ውጤት አሁን እያየነው ነው። ሹመት በዕውቀት ሳይሆን በፓርቲ አባልነትና በትውውቅ ስንሰጥ ከርመን፣ ዛሬ በሚያሳፍር ሁኔታ ምን መወሰን እንዳለብን ቆርጦ የሚናገር አዋቂና ደፋር ባናገኝ አይገርምም። እስካሁን በብድርም ይሁን በልገሳ ያገኘናቸውን ገንዘቦች በማይረባ ዲስኩርና ስብሰባ ስንበትናቸው ከርመን፣ አሁን የሳይንስና ምርምርን ፋይዳ በቁጭት እያየነው ይሆናል። ትላንት በጥቅም ይዞ የሚያጎበድድና ሁሉን እሺ የሚል ለሆዱ የሚሞት ሰውን እየቀጠሩ ወንበራቸውን ያስጠበቁ፣ ዛሬ መፍትሄ ሲፈለግ ድምጻች አጥፍተው ወደ ጉድጓዳቸው ገብተዋል። ዛሬ እስኪ እስካሁን የኖርንበተን ዘይቤ ዘወር ብለን እንይና ወደ እውነታው እንመለስ። ዕውቀት፣ተጠያቂነትንና ለእውነት ፊት ለፊት መጋፈጥ ምን ያህል ከእንደዚህ ዓይነቱ የጉድ ጊዜ ሊታደጉን ይችሉ እንደነበር ዞር ብለን እናስተውል። በግሌ እንስራ ኧረ እባካችሁ እንስራ እያልኩ ሃገሬ ከመጣሁ በኋላ በሳይንሱ ዘርፍ ብዙ ታግያለሁ፣ የሚገርመው ግን የተባልኩት አርፈህ ደሞዝህን እየበላህ ኑር፣ ብር አልተከለከልክ የምን መሟገት ነው ካልሰራሁ ብለህ፣ አግኝተህ ነው ሳትሰራ ደሞዝ ማግኘት ነበር። መቼም አሁን የእንስራ ንዝነዛዬና መጋፈጤ ይገባቸዋል ብዬ አስባለሁ።

አገሪቷንም ለሚመሩት የማስተላልፈው፣ አሁን ለኢትዮጵያ የሚያስፈልጋት በዕውቀት ላይ የተመሰረት ውሳኔ እንጂ በመልካም ቃል የታጀበ ዓረፍተ ነገርና ፖለቲካዊ ሃተታ አይደለም። ሕዝቦች በአሰቃቂ ሁኔታ በበሽታ እንዳያልቁ በፍጥነት በየቀበሌው የችግረኞችና አቅም የሌላቸውን ወገኖች አድራሻ ለይቶ፣ ለነርሱም በተወሰነ ቀን ራሽን የማድረስ መርሃ ግብር አውጥቶ በተቻለ ፍጥነት ወደ ሙሉ እንቅስቃሴን ማቆም መግባት ይበጀናል።

በነገራችን ላይ ትምህርት ቤትን ዘግቶ፣ ስራን ከፍቶ፣ ከዛም የመንግስትን ስራ ዘግቶ የግል ድርጅቶች ከፍቶ፣ ገበያው ደርቶ ትራንስፖርት እንደወትሮው ቀጥሎ ባለበት ሁኔታ አገሪቷ አይደለም ከወረርሽኙ ልትድን ቀርቶ ከሁለት ያጣች የሚያደርግ ውሳኔ መሆኑን ሳልጠቅስ አላልፍም። መካሪም ተመካሪም የሌለባት አገር ይሏል ይሄ ነው። ከሁሉም ግን የሚያስፈራኝ የአፍሪካ መሪዎች ምዕራባውያኑን ለማስደሰትና እርጥባንን ለማግኝት ብለው ልምና በለመደው ባህርያቸው ለምነው የክትባቱን ስራ በአፍሪካ እንዳያስጀመሩት ብቻ ነው።

እግዜር ምህረቱን ለዓለም ሕዝብ ሁሉ ያውርድልን ለኛም የሚያስብ አእምሮ ይስጠን።
አማኑኤል ብሩ ዶ/ር

Tuesday, May 29, 2018

ቀላል ግን የማይቃለል ደግሞም ከባድ ግን የማይካበድ


“እናንተ ሸክማችሁ የከበዳችሁና የደከማችሁ ሁሉ ወደ እኔ ኑ ፤ እኔም ዕረፍት እሰጣችኋለሁ። ቀነበሬን ተሸከሙ፤ ከእኔም ተማሩ፤ እኔ በልቤ የዋህና ትሁት ነኝና ፤ ለነፍሳችሁ ዕረፍት ታገኛላችሁ፤ ቀንበሬም ልዝብ ሸክሜም ቀላል ነውና።” ማቴዎስ 11፡28 — 29

ክርስቲያን ለመሆን በጣም ቀላል ነው። ይኽውም ፈላስፋ፣ የተማረ፣ ብዙ ያነበበ፣ ብዙ ሰው ማወቅ ወይ ደግሞ ሌላ ሌላ መሆን አያስፈልግም። በቃ ክርስቶስ የእግዚአብሄር ልጅ መሆኑን ብናምን በአፋችንም ብንመሰክር ድነን ክርስቲያን መሆን ብቻ ነው። የወህኒ ቤቱ ጠባቂ በሓዋርያት ስራ ምዕራፍ 16 ቁጥር 30 ላይ እነ ጳውሎስን “እናንተ ሰዎች እድን ዘንድ ምን ላድርግ” ሲላቸው የነገሩት እጅግ በጣም ቀላል ነገር ነው፣ “በጌታ በኢየሱስ እመን አንተና ቤተ ሰዎችህ ትድናላችሁ” በቃ ሌላ የተወሳሰበ ነገር የለውም። ወንጌል ውስብስብ አይደለም፣ ወንጌል ቀላል ነው። ጌታ ኢየሱስም ለዚህ ነው “ወደ እኔ ኑ” ብቻ ያለው። ወደ እኔ እንደዚህ ወይም እንደዚያ ሆናችሁ ኑ አላለም እንዳላችሁ ከነ ከበዳችሁ ነገር ከነ ድካማችሁ ኑ ነው ያለን። ያልተወሳሰበ ቅድመ ሁኔታ የሌለበት ጥሪ።  ማወቅ ያለበን አንድ ነገር ብቻ ነው፤ ዕረፍት መፈለጋችንን ብቻ። ሸክማችሁንና ደከማችሁ እኔ ላይ ጣሉትና እኔ የማሸክማችሁን ቀንበርና ሸክም ተሸከሙ፣ የእናንተን በእኔ ለውጡ ይለናል። ማወቅ ያለብን ዋና ነገር ክርስቶስ ጋ ስንመጣ ሸክማችን የከበደንና ደካሞች መሆናችንን በደንብ ማወቅ ከዛም የኛን ጥለን እርሱ የሚያሸክመንን ደስ ብሎን መሸክም እንዳለብን ነው። የራሳችንን ሸከምና የእርሱን ሸክም አንድ ላይ ይዘን መሄድ እንደማንችል ልብ ብለን መገንዘብ ይኖርብናል። ክርስትና ውሳኔን የሚጠይቅ ተረድተነው የምንገባበት የግል ጉዳይ ነው፤ ማቴዎስ 8፡ 18 — 22 እና ሉቃስ 14፡25—35። በቡድን የምንወስነው፣ ሌላው ስለገባ የምንገባበት ወይ ደግሞ ወላጆቻችን ስለሆኑ እኛም የምንሆነው ነገር እንዳይደለ ማወቅ ግድ ይለናል። የደከምን የከበደን ሁሉ ወደ እርሱ ስንመጣ ዕረፍት እናገኛለን፣ ዕረፍቱ ግን የሚገኘው መስቀሉ ስር ሸክማችንን ከጣልን በኋላ ከእርሱ ስንማር ነው። እርሱ የሚያሸክመንን ቀንበር መያዝ የምንችለው ከእርሱ ስንማር ነው። የእርሱን ማንነት ስናውቅና ስንቀበለው ዕረፍት እናገኛለን። ክርስቶስ ከእኔ የምትማሩት “የዋህነትና ትህትና” ነው ይለናል።

በዚህ ዓለም ስንኖር ክርስቲያን ለመሆን ቀላል፤ ነገር ግን ክርስቲያን መሆን ከባድ ነው። ይህን ያልኩበትም ምክንያት የክርስቶስን ህይወትና አስተምሮ ስናይ ከምንኖርባት ዓለም አካሄድ ጋር የማይገናኝ እንዳውም የሚቃረን ሆኖ እናገኘዋለን። ክርስቶስን ከእኔ ተማሩ የሚለንን እስኪ እንይ። የማቴዎስ ወንጌል ላይ ከምዕራፍ 5 እስከ 7 ክርስቶስ የእርሱ የሆኑት ወይም የእርሱን ቀንበር የተቀበሉት ምን ዓይነት ሰዎች ሊሆኑ እንደሚገባቸው ያስተምራል። በምዕራፍ 5 የተራራው ስብከት ከሚባለው ተነስቶ ስለ መግደል፣ ሰለ ማመንዘር፣ ስለ መሓላ፣ ስለ መቀበል፣ ስለ ምጽዋት አሰጣጥ፣ ስለ ጸሎት፣ ስለ ሀብት፣ ስለ ጭንቀት እና ሌሎች ነገሮች ያስተምራል። በእውነት ለመናገር ለመተግበር ከባድ የሆኑ አስተምህሮዎች ናቸው። ከባድ የሆኑበትም ምክንያት ከዚህ ዓለም የኑሮ አካሄድ ጋር ስለሚጣረሱ ነው። ታድያ ክርስትና ዕረፍት የሚሰጥና ሸክሙ ቀሊል ከሆነ፣ ለምን ስንተገብረው ይከብዳል፣ ለምን እንሰደድበታለን ለምንስ መከራ እንቀበልበታለን ይህ ጥያቄ ትክክለኛ ጥያቄ ነው። ምንአልባትም ሁላችንም በህይወታችን ውስጥ የሚሆነውን አይተን ደጋግመን ጠይቀን ይሆናል።

ለዚህም ነው ርዕሱን “ቀላል ግን የማይቃለል ደግሞም ከባድ ግን የማይካበድ” ያልኩት። ይህን ሁለት ፈርጅ ያለውን ሃሳብ ከመተንተኔ በፊት አንድ እውነታ ላካፍላችሁ። ኢየሱስ ለፈሪሳውያን ታልፎ ከተሰጠ በኋላ በስቅለት ቀን ከባድ ስቃይ ተቀብሏል። በሁለት አበይት ምክንያት፥ 1 እኛን ከአብ ጋር ሊያስታርቅ፣ 2 ከዓለም ጋር የማይስማማ ትምህርት ስለነበረው ነው። ስለ ክርስቶስ የመስቀል ስቃይ ያጠኑ የመጽሓፍ ቅዱስ ምሁራን በስቅለት ቀን ኢየሱስ 39 ጊዜ ተገርፏል ይላሉ፣ በጣም ሲያብራሩትም 13 በደረቱ ላይ  26 ደግሞ  በጀርባው ላይ በጅራፍ ተገርፏል ይላሉ። በዘመኑ በአይሁድ ህግ ትልቁ ግርፋት 40 ነበረ። አንዳንድ ጥናቶች ላይ ኢየሱስ 100 ጊዜ እንደተገረፈ ይናገራሉ። ይኽውም በጊዜው የነበረው የሮማውያን ህግ ምንም የግርፋት ቁጥር ልክ ስላልነበረው፣ እናም የክርስቶስ አስከሬን ተከፍኖበት የነበረውን አሁን ድረስም በጣልያን ቱሪን የሚገኘውን ጨርቅ “Shroud of Turin” ያጠኑ ሰዎችም የሚስማሙበት 100 መገረፉን ነው። ከዛም በላይ ክርስቶስ ዋና የምንላቸው በካቶሊኩም ዓለም “አምስቱ ቅዱስ ቁስሎች” ተብለው የሚታወቁ ቁስሎችን የቆሰለበት የስቅለትን ጊዜ ስናስብ ብሎም ከነ ግርፋቱ ለስድስት ሰዓታት በመስቀል ላይ መቃተቱን ስናስብ፤ ክርስትና ለመቀበል ቀላል ስለሆነ ክርስቶስ ለኛ ዕረፍትን ለመስጠት የከፈለው ግን ቀላል እንዳልሆነ ማወቅ ግድ ይለናል። ለዚህ ነው ክርስትና ቀላል ግን የማይቃለል የሆነው። ደግሞም እርሱ ለኛ ብሎ ያሳለፈው መከራና ስቃይ ሲገባን፣ እኛ ለእርሱ ብለን የምንቀበለውን መከራ እንዳናካብድ ግድ ይለናል። ስለዚህ ክርስትና ከባድ ግን የማይካበድ የሆነው። ከዛም አልፈን የአዲስ ኪዳን ሐዋርያት ስለ ክርስቶስ ያሳለፉትን መከራ እና ስቃይ ስናይ ደግሞም በዚህ ዘመን በክርስቶስ ምክንያት ክርስቲያኖች የሚያልፉበት መከራ በደንብ ብናጤነው፣ በዕውነት እኛ የምናልፍበት መከራ የማይካበድ መሆኑ ይገባናል። 2 ቆሮንቶስ 11፡16 — 33 ላይ ጳውሎስ በዝርዝር ስላለፈበት መከራ ጽፏል። ለጢሞትዮስም ሲመክረው “በእርግጥም በክርስቶስ ኢየሱስ በእውነተኛ መንፈሳዊ ሕይወት መኖር የሚወዱ ሁሉ ይሰደዳሉ።” ይለዋል። እንዲሁም 2 ቆሮንቶስ ላይ “ስለ ክርስቶስ በድካም፣ በስድብ፣ በመከራ፣ በስደትና በጭንቀት ደስ የምሰኘው ለዚህ ነው፤ ስደክም ያን ጊዜ ብርቱ ነኝና።” ይላል። ጴጥሮስም እንዲሁ በመጀመርያ መልዕክቱ ምዕራፍ 3፡18—22 እና ምዕራፍ 4፡12—19 ክርስቲያን በመሆን ስልሚደርስ መከራ ይነግረናል።

በትንሳኤው ደግሞ የገለጠልን፣ በብዙ ስቃይ እና መከራ ያለፈው ይህ ጌታ በቃ አለቀ አሸነፍነው ሲሉ ድንገት ሳያስቡት በሶስተኛው ቀን ሞትን ድል አድርጎ የሲኦልን መክፈቻ ይዞ ተነሳ። ምን መከራው ቢበዛ፣ ስቃዩ የማያልፍ ቢመስል፣ ተሸነፈ አለቀለት የሚያስብል ሁኔታ ቢፈጠር ድል አድራጊው ጌታ በሰዓቱ ጊዜውን ጠብቆ በሶስተኛው ቀን በድል እንደተነሳ፣ እርሱን ለማክበር ብለው በመከራ ለሚያልፉትም በጊዜውና በሰዓቱ ሳይዘገይ ወይም ሳይፈጥን በትንሳኤው ሃይል ይመጣላቸዋል። ጳውሎስ አሁንም በ 2 ቆሮንቶስ 4 ላይ “ከየአቅጣጫው ብንገፋም አንንኮታኮት፤ ግራ ብንጋባም ተስፋ አንርቆጥም፤ ብንሰደድም ተጥልን አንቀርም፤ መትተው ቢጥሉንም አንጠፋም” ያለው። ለእርሱ ከተገዛንና የዓለምን ብልጭልጭ ነገር ንቀን በመንፈሳዊ ህይወታችን እርሱን ለመምሰል ከቆረጥን ነገር ሁሉ ለበጎ እንዲደረግ እንወቅ።

ስለዚህ ክርስትና ቀሎብን ከሆነ መስቀሉን እንይ፤ ደግሞም ክርስትና ከብዶብንም ከሆነ መስቀሉን እንይ። የዛን ጊዜ ቀላል ግን የማይቃለል ደግሞም ከባድ ግን የማይካበድ ይሆንልናል። ክርስትና ከድል ጀምረን የምንኖረው እንጂ ድል ለማድረግ ገና በራሳችን የምንታገለው እንዳልሆነ እንዲገባን ትንሳኤውን እናስተውል። ደግሞም ኢየሱስ እንዲህ ብሎናል፥ “በእኔ ሰላም እንዲኖራችሁ፣ ይህን ነግሬአችኋለሁ። በዓለም ሳላችሁ መከራ ኧለባችሁ፤ ነገር ግን አይዟችሁ፤ እኔ ዓለምን አሸንፌዋለሁ።” ማቴዎስ 5፡11 — 12

Sunday, April 1, 2018

እውነተኛ ክርስትና ምንድን ነው?

በማግሥቱ ከቢታንያ ሲወጡ ኢየሱስ ተራበ። እርሱም ቅጠል ያላት የበለስ ዛፍ ከሩቅ አየ፤ ምናልባት ፍሬ ይገኝባት እንደሆነ ብሎ ወደ እርሷ መጣ፤ ነገር ግን የበለስ ወራት አልነበረምና ከቅጠል በቀር ምንም አላገኘባትም። ከዚያም ዛፏን፣ “ከአሁን ጀምሮ ለዘላለም ማንም ፍሬ ከአንቺ አይብላ” አላት። ደቀ መዛሙርቱም ይህን ሲናገር ሰሙ። ወደ ኢየሩሳሌምም መጡ፤ ከዚያም ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ፣ የሚሸጡትንና የሚገዙትን ያስወጣ ጀመር። የገንዘብ መንዛሪዎችን ጠረጴዛና የርግብ ሻጮችን መቀመጫ ገለባበጠ፤ ማንም ዕቃ ተሸክሞ በቤተ መቅደሱ ቅጥር ግቢ ውስጥ እንዳያልፍ ከለከለ። ሲያስተምራቸውም፣ “‘ቤቴ ለሕዝቦች ሁሉ የጸሎት ቤት ይባላል’ ተብሎ አልተጻፈምን? እናንተ ግን የሌቦች ዋሻ አደረጋችሁት!” አላቸው። የካህናት አለቆችና ጸሐፍትም፣ ይህን ሲሰሙ እንዴት እንደሚያጠፉት መንገድ ይፈልጉ ጀመር፤ ሕዝቡ ሁሉ በትምህርቱ በመገረማቸው ፈርተውታልና። በመሸም ጊዜ ከከተማዪቱ ወጥተው ሄዱ። የማርቆስ ወንጌል 11 ፥ 12 — 19

በዚህ ክፍል ውስጥ ኢየሱስ ሁለት ነገሮችን ሲያደርግ እንመለከታለን 1 ፍሬ ያላፈራችውን የበለስ ዛፍ ሲረግማትና 2 ለሁለተኛ ጊዜ ቤተ መቅደስ ውስጥ ገብቶ ነጋዴዎችን ሲያስወጣ እንመለከታለን። ሁለቱንም ድርጊቶች የፈጸመው የህማማት ሳምንት ተብሎ በሚገለፀው ሳምንት ውስጥ ነው። ሁለቱም ድርጊቶች አንድ አይነት ሃሳብ አላቸው ብዬ አምናለሁ። እስኪ ሁለቱንም በተራ እንመልከታቸው።

1 ፍሬ ያላፈራችውን የበለስ ዛፍ፦ የበለስ ዛፍ በተፈጥሮው ሰፋፊ ቅጠሎች ያሉት፣ ስሩ በጣም ጥልቅና ውሃን ከሩቅ ቦታ ስቦ ማምጣት የሚችል ሲሆን፣ ፍሬውና ቅጠሉ እኩል ነው የሚወጡት። በብሉይ ኪዳንም የበለስ ዛፍ የእስራኤል ብሔራዊ ምልከት ነበር። ክርስቶስ ፍሬ አገኛለሁ ብሎ ወደ ዛፏ የተጠጋው ቅጠሎቿን ከሩቅ አይቶ ነበር። ነገር ግን ፍሬ አጥቶባት ዳግመኛ እንዳታፈራ ሲረግማት እናያለን። በማግስቱ ጠዋትም ደቀ መዛሙርቱ ደርቃ አይተዋት ተገርመው ሲጠይቁት ስለ እምነት ሲያስተምራቸው በሚቀጥለው ክፍል ላይ እናያለን። እዚህ ክፍል ላይ የምንታዘበው የበለስ ዛፍዋን አስመሳይነት ነው። ፍሬ እንዳለው የበለስ ዛፈ በቅጠሎች ብቻ የታጀበች ነገር ግን ምንም ፍሬ የሌላት። ከዚህም ጋር ሌላ ተያይዞ የምናየው ጠቅላላ እስራኤል እንደ መንግስት ፍሬ አልባ ከሃይማኖተኝነት በቀር መንፈሳዊ መካን እንደሆነች በምሳሌአዊ ዘይቤ የሚያስረዳ ድርጊት ኢየሱስ እንደተናገረ የሚገልጽም አሉ።

2 የክርስቶስ ቤተ መቅደሱ ማንፃት፦ ቤተ መቅደሱ የፋሲካ በዓል በመድረሱ ብዙ ሰዎች የመንፃት ስርዓትን ለመፋጸም የሚመጡትን ሰዎች በማሰብ በቤተ መቅደሱ አካባቢና ውስጥ ይሸጡና ገንዘብ ይለውጡ ነበር። እነዚህ ነጋዴዎች የህዝቡን ልብ ያወቁና ጊዜውንም ተጠቅመው ብዙ ትርፍ ለግላቸው ሰብስበው ለመሄድ የመጡ እንጂ፣ ለህዝቡ ወይም ለእግዚአብሔር ቤት አስበው የመጡ እንዳልነበሩ በግልጽ ይታያል። ቤተ መቅደሱንም ካፀዳ በኋላ ኢየሱስ ቤተ መቅደሱን ለትክክለኛ ተግባር ሲያውለው እናያለን፣ ይኽውም ለማስተማርና እውነተኛ ፈውስ የሚፈልጉን በነፃ መፈወስ ነበር። ማቴዎስ 21 ፥ 12 — 15 ይመልከቱ።
እነዚህ ሁለት የኢየሱስ ድርጊቶች አስመሳይ የሆነ ወይም እውነታኛ ያልሆነን ክርስትና ከሩቅ በሚታዪ አማላይና ሃይማኖታዊ ነገሮች የታጀበ ነገር ግን ሲጠጉት ፍሬ ቢስ የሆነና፣ ሁኔታንና አመቺ ጊዜን ተጠቅሞ ግላዊ ጥቅምን ብቻ የሚሳድዱትን እየተቃወመ እንደሆነ ያሳዪናል። እንግዲህ ይህን ነገር ወደ ራሳችን፣ ወደ ቤተክርስትያናችን፣ ወደ ሃገራችንና ብሎም ወደ ዘመናችን ስናመጣው እንዲህ ብለን ራሳችንን መጠየቅ ይኖርብናል። ፍሬ ያለው እውነተኛ ክርስትያን ነኝን ሁኔታንና አመቺ ጊዜን ተጠቅሜ ግላዊ ጥቅሜን ብቻ የሚሳድድ ነኝንእውነትኛ ፍሬ ያለው ክርስቲያን አስመሳይና ሁኔታንና አመቺ ጊዜን ተጠቅሞ ግላዊ ጥቅምን ብቻ የሚሳድድ ሊሆን በፍፁም  አይችልም። እውነትኛ የመንፈስ ፍሬዎች በገላትያ መጽሃፍ ምዕራፍ 5፡22 — 26 ላይ ተጠቅሷል። የሥጋ ፍሬዎችም እነደዚሁ በገላትያ መጽሃፍ ምዕራፍ 5፡19 — 21 ላይ ተጠቅሷል። ታድያ እነዚህን እውነትኛ የመንፈስ ፍሬዎች ለማፍራት ምን ማድረግም እንዳለብን በዪሐንስ 15 ላይ በግልጽ ተጽፏል። የዪሐንስ 15 ዋና መልዕት እውነትኛ የመንፈስ ፍሬዎች ለማፍራት ከግንዱ መጣበቅ እንዳለብን ይተነትናል፣ ይህም ግንድ እራሱ ክርስቶስ እንደ ሆነ ተገልጿል። ከግንዱ መጣበቅስ ምን ማለት ነው እንዴት ነውስ የምንጣበቀውበዪሐንስ 15 ቁጥር 17 ላይ በግልጽ ተጽፏል፣ እንዲህም ይላል “እርስ በእርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ ትዕዛዜ ይህቺ ናት”። ስለዚህም በግንዱ ላይ መጣበቅ ማለት በፍቅር መኖር ማለት ነው፣ በዪሐንስ 15 ቁጥር 9 ላይ “አብ እንደ ወደደኝ ሁሉ እኔም ወደድኋችሁ፤ በፍቅሬ ኑሩ” ተብሎ ተጽፏል። ስለዚህ እውነትኛ የመንፈስ ፍሬዎችን ለማፍራት ፍቅር ቁልፉ ነው ማለት ነው። ለዚህም ነው ክርስቶስ እንዚህን ሁለት ነገሮች ባደረገበት ሳምንት በመስቀል ላይ የፍቅርን ጥግ ያሳየን። በዪሐንስ 15 ቁጥር 13 ላይ “ስለ ወዳጆቹ ሕይወቱን አሳልፎ ከመስጠት የሚበልጥ ፍቅር ለማንም የለውም።” ይላል። ዳዊትም በመዝሙር 63፡3 “ፍቅርህ ክህይወት ይበልጣልና ከንፈሮቼ ያመሰግኑሃል።” ይላል።

ክርስቶስም በማርቆስ 12፡28 – 34 ላይ ስለ ታላቁ ትዕዛዝ ይናገራል። “ኢየሱስም እንዲህ ሲል መለሰለት፤ “ከሁሉ የሚበልጠው ይህ ነው፤ እስራኤል ሆይ ስማ፤ ጌታ አምላካችን አንድ ጌታ ነው፤ አንተም ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ፣ በፍጹም ነፍስህ፣ በፍጹም ሐሳብህና በፍጹም ኀይልህ ውደድ።’ ሁለተኛውም ይህ ነው፤ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ።“ ከእነዚህም የሚበልጥ ትእዛዝ የለም።” በማቴዎስ 22፡40 ላይም “ሕግና ነብያት በሙሉ በነዚህ ሁለት ትዕዛዛት ላይ የተንጠለጠሉ ናቸው።” ብሎ ኢየሱስ ይናገራል። ይህን ሲል ምን ማለቱ ነው፤ እግዚአብሔር አምላክህን ከወደድክ እንዲሁም ጐረቤትህን እንደራስህ ከወደድክ የቀሩትን ትዕዛዛት መፈጸም እጅግ በጣም ቀላል ነው ማለቱ ነው። ስለዚህ እውነተኛ ክርስትና ፍቅር ነው ብለን በአንድ ቃል መግለጥ እንችላለን። ጳውሎስ ስለ እውነትኛ የመንፈስ ፍሬዎች በገላትያ መጽሃፍ ምዕራፍ 5፡22 — 26 ላይ ሲተነትንም “የመንፈስ ፍሬ ግን ፍቅር፣ ደስታ፣ ሰላም፣ ትዕግሥት፣ ቸርነት፣ በጎነት፣ ታማኝነት፣ ገርነት፣ ራስን መግዛት ነው። እንደነዚህ ያሉትንም የሚከለክል ሕግ የለም። የክርስቶስ ኢየሱስ የሆኑት ሥጋን ከክፉ ምኞቱና መሻቱ ጋር ሰቅለውታል። በመንፈስ የምንኖር ከሆን፣ በመንፈስ እንመላለስ። እርስ በርሳችን እየተጎነታተልንና እየተቀናናን በከንቱ ውዳሴ አንመካ።ል። ለዚህ ይሆናል ፍቅርን በአንደኝነት የጠቀሰው። ከዛም በበለጠ ጳውሎስ 1 ቆሮንቶስ ምዕራፍ 13 ላይ በጣም የተብራራ መልዕክት ስለ ፍቅር ጽፏል። 1 ቆሮንቶስ ምዕራፍ 13ትን በተለይ ከቁጥር 4 ጀምሮ ስታንቡት ፍቅር እውነትኛ የመንፈስ ፍሬዎች አጭቆ የያዘ የሁሉም ፍሬዎች መፈልፈያ እንደሆነ ልብ ማለት አያዳግትም። “ፍቅር ታጋሽ ነው፤ ደግሞም ቸር ነው። ፍቅር አይመቀኝም፤ አይመካም፤ አይታበይም፤ ተገቢ ያልሆነ ነገር አያደርግም፤ ራስ ወዳድ አይደለም፤ አይበሳጭም፣ በደልን አይቈጥርም። ፍቅር ከእውነት ጋር እንጂ በዐመፅ ደስ አይሰኝም። ፍቅር ሁል ጊዜ ይታገሣል፤ ሁል ጊዜ ያምናል፤ ሁል ጊዜ ተስፋ ያደርጋል፤ ሁል ጊዜ ጸንቶ ይቆማል።

ፍቅር ከቶ አይወድቅም፤ ነገር ግን ትንቢት ቢሆን ይሻራል፤ ልሳንም ቢሆን ይቀራል፤ ዕውቀትም ቢሆን ይሻራል። ምክንያቱም የምናውቀው በከፊል ነው፤ ትንቢት የምንናገረውም በከፊል ነው። ነገር ግን ፍጹም የሆነው ሲመጣ በከፊል የነበረው ይሻራል።”
ስጠቀልለው እውነተኛ ክርስትና ማለት በፍቅር መመላለስ ማለት ነው። ወይም ደግሞ እውነተኛ ክርስትና በአንድ ቃል ግለጹት ከተባልን “ፍቅር” ብለን መግለጸ እንችላለን። ደግሞም ኢየሱስ ይህን ፍቅር በተግባር አሳይቶናል። በፍቅር በመኖር፣ እርስ በርሳችን በመዋደድ፣ አልፎም ጠላቶቻችንን በመውደድ ፍሬ ያለው እውነተኛ ክርስትናን እንኑር፣ አስመሳይ፣ ሁኔታንና አመቺ ጊዜን ተጠቅመን ግላዊ ጥቅምን ብቻ የሚሳድዱ ክርስቲያኖች ከመሆንም ከእንደዛ አይነቶቹም እንጠበቅ።

ጸሓፊውም እንዲህ አለው፤መምህር ሆይ፤ መልካም ብለሃል፤ እርሱ አንድ መሆኑን፣ ከእርሱም ሌላ አለመኖሩን መናገርህ ትክክል ነው፤ እርሱን በፍጹም ልብህ፣ በፍጹም አእምሮህ፣ በፍጹም ነፍስህ፣ በፍጹም ኀይልህ መውደድ፣ እንዲሁም ባልንጀራህን እንደ ራስህ መውደድ ከሚቃጠል መሥዋዕት ሁሉና ከሌሎችም መሥዋዕቶች ይበልጣል።”“ ማርቆስ 12፡ 32 — 33